Categories

A sample text widget

Etiam pulvinar consectetur dolor sed malesuada. Ut convallis euismod dolor nec pretium. Nunc ut tristique massa.

Nam sodales mi vitae dolor ullamcorper et vulputate enim accumsan. Morbi orci magna, tincidunt vitae molestie nec, molestie at mi. Nulla nulla lorem, suscipit in posuere in, interdum non magna.

«የሃይማኖት መሪዎች፥ ምሁራን፥ የሀገር ሽማግሌዎች፥ መንግሥትም አንድ ላይ ተሰብስበን ብሔራዊ ዕርቅ መደረግ አለበት።» (ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል)

(ሪፖርታዥ በመልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው)ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል በአሁኑ ወቅት የዋሺንግተንን እና የካሊፎርኒያን ሁለት አኅጉረ ስብከቶች በሊቀ ጳጳስነት እየመሩ ይገኛሉ። ከሁሉም ጋር ተስማምተው ስለሚያገለግሉ ምንም ድምፅ አይሰማም። በትህትናቸውና በትእግሥታቸው ሁሉንም አሸንፈዋል። ለሐዋርያዊ አገልግሎት በተገኙበት አጥቢያ ሁሉ ይቀድሳሉ፥ ያስተምራሉ። ስብከታቸው ሁሉንም የሚማርክ ዘመኑን የዋጀ ነው። መድከም፥ መሰልቸት የለም፥ ሁልጊዜ አየር ላይ ናቸው። በየጊዜውም አዳዲስ አጥቢያዎች እየተጨመሩ ነው። ከብዛታቸው የተነሣ በተለይም በክብረ በዓላት፡-አንድ ቦታ ቅዳሜ ቀን ቀድሰው፥ አስተምረውና አንግሠው ምሽቱን ደግሞ ወደ ሌላ ስቴት ይበራሉ። በማግስቱ እሑድም ቀድሰው አስተምረው ያነግሣሉ። እረፍት የሚባል ነገር የላቸውም፥ እረፍት የሚሰማቸው እንደ መላእክት ሲያገለግሉ ነው።
ብፁዕ አባታችን ሀገርን በተመለከተ የግንባር ሥጋ ናቸው። በዐውደ ምሕረት ያስተምራሉ፥ መግለጫ ያወጣሉ፥ ሀገሬ እንዴት ውላ እንዴት አድራ ይሆን? ብለው ዕለት ዕለት ይከታተላሉ፥ ይጸልያሉ። ስለ ሕዝቡ ይጨነቃሉ፥ ያዝናሉ። ምክንያቱም በአባትነት ወንበር የተቀመጡት፥ ተቀብተው የተሾሙት ለዚህ ነውና። የተሾሙበትን ዓላማ ስለሚያውቁም የሚፈሩት የሚያፍሩት የላቸውም። በተለይም ባለፈው ዓመት ከችግሩ ስፋት የተነሣ ሀገራችን በኮማንድ ፖስት ስር ወድቃ፥ እውነትን የሚተነፍስ ሁሉ በሚታሰርበት ወቅት፥ ስለ ሀገሪቱ ችግርና ስለ ሕዝቡ ሥቃይ በቅዱስ ሲኖዶስ ላይ ሪፖርት ያቀረቡ ብቸኛው ሰው ናቸው። አሁንም ሀገሪቱ በተቃውሞ ምስቅልቅሏ በወጣበት በዚህ ሰዓትም ከአደባባይ የጡመራ መድረክ አዘጋጅ ከመልአከ ኤዶም ቀሲስ ኤፍሬም እሸቴ ጋር ቃለ ምልልስ አድርገዋል። (https://youtu.be/t-7T3wnda5k)
“ደርሶ ይጦረኛል ያለችው ልጅ ሲሞት ….. ሰው ሠራሽ ሕንፃ ቢፈርስ መልሶ መገንባት ይቻላል፥ ሕንፃ እግዚአብሔር የሆነ የሰው ልጅ ሲፈርስ ግን እንደገና መመለስ አይቻልም። ደግሞም ሕንፃ እግዚአብሔርን ማፍረስ ኃጢአት ነው። ይላል። ፩ኛ፡ቆሮ፡ ፫፥ ፲፮። በመሆኑም ከሰው ፍርድ ማምለጥ ቢቻል ከእግዚአብሔር ፍርድ ማምለጥ አይቻልም። እኔ እየሆነ ባለው ነገር እጅግ በጣም አዝናለሁ። እናት ልጄ ደርሶ ይጦረኛል ብላ ስትጠበቅ አስከሬኑ ተጭኖላት ሲመጣ ለማንም ቢሆን ያሳዝናል። ….. በክልሎች መካከል ያለው ልዩነት ያመጣው ሞትና መፈናቀል፥ በየከፍተኛ ትምህርት ተቋማቱ ያለው እርስ በርስ መገዳደል የአደጋውን ከፍተኛ ደረጃ መድረስ ቍልጭ አድርጎ ያሳያል። ይኸንንም መንግሥት ራሱ አልካደውም፥ ሀገሪቱ አደጋ ላይ ናት ብሎ መግለጫ አውጥቶአል። በሀገር ውስጥም በውጭ ሀገርም የሚገኙ የፖለቲካ ድርጅቶች፥ የሃይማኖት ተቋማት፥ ታላላቅ ምሁራን፥ የሰብአዊ መብት ተከራካሪዎች፥ የአሜሪካ መንግሥት፥ የአውሮፓ ኅብረት ወዘተ . . . አስጊነቱን እየተናገሩ ነው። በሀገራችን በኢትዮጵያ ከጥንት ጀምሮ ግጭቶች እንደነበሩ ይታወቃል። በግጦሽ መሬትና በመሳሰሉ ነገሮች ሕዝቡ እርስ በርስ ይጋጭ ነበር። የአሁኑን ልዩ የሚያደርገው ሀገሪቱ በዘርና በቋንቋ ተሸንሽና ግጭቱ እስከ ጦርነት ድረስ ማደጉ ነው። ያለንበት ዘመን ኢትዮጵያዊነት ዝቅ፥ ጎሳ ደግሞ ከፍ ተደርጎ የተሰበከበትና የተራገበበት ዘመን ነው። በቀበሌ መታወቂያ ላይ ሳይቀር ዜግነት የሚለው ተፍቆ ብሔር የሚለው የተተካበት ጊዜ እንደሆነ እናውቃለን። ይህም ሕዝቡን ለዘር ግጭትና ፍጅት ያመቻቸዋል። ትናንትም ሆነ ዛሬ ኢትዮጵያውያን ከየክልሉ እንዲፈናቀሉ የተደረገው መታወቂያቸው እየታየ ነው።
….. የሩዋንዳና የሶማልያ ዕድል ይገጥመናል ብዬ አላስብም፤ ….. እርግጥ ሁኔታው ሲታይ የሚያሰጋ ነገር አለው። ይሁን እንጂ ኢትዮጵያ ሀገረ እግዚአብሔር ስለሆነች፥ ለከፋ ነገር አሳልፎ አይሰጣትም ብዬ አምናለሁ። በተጨማሪም የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም የዓሥራት ሀገር በመ ሆኗ በአማላጅነቷ ትጠብቃታለች የሚል እምነት አለኝ። ከዚህም ሌላ ሀገሪቱ እንደ ሩዋንዳ እና እንደ ሶማልያ የማትሆንበት ሁለት አሳማኝ ምክንያቶች አሉኝ። ፩ኛ/የኢትዮጵያ ሕዝብ ሃይማኖተኛ በመሆኑ ምን ቢገፋፉት ወደ ባሰ ነገር አይገባም። ይህ ሕዝብ ፳፭ ዓመት ሙሉ ያል ተነገረው ነገር የለም። እገሌ የሚባል ብሔር እንዲህ አድርጎህ፥ እንዲህ ጨቁኖህ እያሉ ቀስቅሰውታል። እንደ ቅስቀሳው ቢሆን ኖሮ ገና ድሮ ሩዋንዳን እና ሱማልያ በሆነች ነበር። በየቤተ እምነቱ የሚሰበከው ሰላምና ፍቅር በመሆኑ፥ አንዳንድ ጥፋቶች ቢኖሩም ሕዝቡ የከፋ ነገር ከማድረግ ተቆጥቦአል። እርግጥ እኛ ያልነው ካልሆነ፥ እኛ ከሌለን ሀገሪቱ ትፈርሳለች የሚሉ ክፍሎች አሉ። እነርሱ ይህን ይበሉ እንጂ ሀገረ እግዚአብሔር ኢትዮጵያ አትፈርስም። ደግሞስ ኢትዮጵያን የሚያፈራርሳት በዘር መለያየት ነው ወይስ አንድ መሆን? ማንም ሰው የመሰለውን ሊናገር ይችላል፥ እግዚአብሔር ግን ኢትዮጵያን አይተዋትም። ፪ኛ/“ሕዝቡ የተለያየ ቋንቋ ይናገር እንጂ በደምና በአጥንት የተሳሰረ ሕዝብ ነው፥ በጋብቻ ተዋሕዷል፥ ከሁለትና ከሦስት ዘር የተወለደ ይበዛል። ከዚህም ጋር በማኅበራዊ ኑሮ እርስ በርሱ ተሳስሯል፥ በዕድር በእቍብና በደቦ ይገናኛል፥ በአበልጅነት ተዛምዷል። ስለዚህ ተለያይቶ የማይለያይ ሕዝብ ነው። በዚህ በማይለያይ ሕዝብ መካከል ጠብን መዝራት እግዚአብሔርን ማስቆጣት ነው። ” ይላል። ምሳ፡፮፥ ፲፮።
… “ችግር መፍጠር ቀላል ነው፤” ….. “በማናቸውም ቦታና ጊዜ ችግር መፍጠር እጅግ በጣም ቀላል ነው፥ የተፈጠረውን ችግር መፍታት ግን ከባድ ነው። ትእግሥትና ጥበብ ይጠይቃል። በሀገራችን ለተፈጠረው ችግር የቤተ መንግሥቱም የቤተ እምነቶችም እጅ አለበት፥ ማንም ነጻ አይደለም። መንግሥት እኮ ከሌላ ፕላኔት የመጣ ልዩ ነገር አይደለም፥ የወጣው ከሕዝቡ መካከል ነው። በመሆኑም ሕዝቡ መብቱን በሚጠይቅበት ጊዜ አፋጣኝ እና አጥጋቢ መልስ መስጠት አለበት። ሕዝቡ ብዙ ብሶት አለበት፥ ብሶቱንም በተለያየ መልኩ እየገለጠ ነው። የከፍተኛ ት/ት ተቋማት ተማሪዎችና መምህራን፥ ገጣሚያን፥ ቀልድ አቅራቢዎች፥ የትያትር ሰዎች፥ የሥነ ጽሑፍ ሰዎች፥ ሰባኪያን፥ ዓለማውያን ዘፋኞች ወዘተ . . . የራሳቸውንም የሕዝቡንም ብሶት በአደባባይ እየገለጡ ነው። ይኸንን ሁሉ መስማትና ማስተዋል ይገባል። የድሮ መሪዎች፡-“እረኛ ምን ብሎ አንጐራጐረ? አዝማሪ ምን ብሎ ዘፈነ?”እያሉ በመጠየቅ የሕዝቡን ብሶት ያውቁ ነበር። …. “አክራሪ ዘረኝነት ለመኖሩ ሳይንሳዊ ማረጋገጫ የሚያስፈልገው አይደለም፤” ….. “በሀገራችን ያለው ችግር የአንድ ጀንበር ሳይሆን የተከማቸ ችግር ነው፥ በወቅቱ መፍትሔ ተበጅቶለት ቢሆን ኖሮ ከዚህ አይደርስም ነበር። መንግሥትም ከአንጀቱ ይሁን ከአንገቱ ባላውቅም ችግሩን አምኖ አክራሪ ብሔርተኞች አሉ፥ እያለ ነው። ይሁን እንጂ ለሀገሪቱ የሚጠቅማት ችግሩን ማውራት ብቻ ሳይ ሆን ችግሩን ማስወገድ ነው። ሕዝቡ አደባባይ ወጥቶ ችግሩን ሲያሰማ መናቅ የለበትም። ካለፉት መንግሥታት መማር ያስፈልጋል። የዓፄ ኃይለ ሥላሴንም ሆነ የደርግን መንግሥት የጣላቸው ሕዝብ ነው። ሕዝብ በየአደባባዩ የሚጮኸው የለውጥ አምሮት ኖሮበት ሳይሆን ሰብአዊ መብቱ እንዲከበርለት ነው። የኑሮ ውድነቱ፥ ሥራ ማጣቱ፥ የነፃነት ረሀብ ጥማቱ ወዘተ . . . አስመርሮታል። ይኸንን ሁሉ በሰከነ አእምሮ መመልከት ያስፈልጋል።
…. በሀገራችን ጎጠኝነት፥ ዘረኝነት፥ ራስ ወዳድነት ለመኖሩ ሳይንሳዊ ማረጋገጫ የሚያስፈልገው አይደለም። በቤተ መንግሥቱም በቤተ ክህነቱም ተንሰራፍቷል። ለእኛ ለሃይማኖት ሰዎች ኢትዮጵያዊነትም ቢሆን የመጨረሻችን አይደለም፥ ከዚያም አልፈን ሰማያዊ ሀገር አለን። ይላል። ፊል፡፫፥ ፳። በክርስትና ት/ት ዘረኝነት የሚወገዝ ነው፥ ምክንያቱም በክርስ ቶስ አንድ አካል ነን። ይላል። ሮሜ፡፲፪፥ ፬። ስለዚህ በዚህ ላይ ተመሥርተን በግልጥ መናገር አለብን። እርግጥ በግልጥ በመናገራችን እንደ ተቃዋሚ ሊያስቆጥረን ይችላል። ምንም ተባለ ምን እውነቱን መናገር ነው፥ ይህ እውነት ለምን ተነገረ ለሚሉትም ጭምር ጠቃሚ ነው። … ከቤተ ክርስቲያን ምን ይጠበቃል …… ቤተ ክርስቲያን በሀገር ጉዳይ ተገቢውን ሥራ እየሠራች ነው ለማለት አልደፍርም። ቸልተኝነት፥ ዝምታ አለ። ይህ ደግሞ ለመንጋው አለመራራት ነው፥ ምንደኛ የሚያሰኝም ነው። ዮሐ፡፲፥ ፲፪። ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን ከእግዚአብሔር የተሰጣትን አደራ ተመልክታ ከፍተኛ ሚና መጫወት ይጠበቅባታል። እርግጥ የሃይማኖት ተቋማት ተወካዮች ተሰብስበው መግለጫ አውጥተዋል። ነገር ግን በቂም አጥጋቢም አይደለም። ይህች ሀገር ከገባችበት ማጥ ውስጥ እንድትወጣ ከተፈለገ ሁሉን አቀፍ ጉባኤ መጠራት አለበት። መንግሥት በየጊዜው ችግሮችን ፈትቻለሁ ቢልም የተፈታ ችግር ስለሌለ ሁሉም ነገር እየባሰበት ነው። ደግሞም በመካከላችን አለመተማመን ነግሦአል ሲል መግለጫ አውጥቶአል። ታዲያ እንዴት አድርጎ ነው መቶ ሚሊዮን ሕዝብ የሚመራው? የማይሆን ነገር ነው። …. የሃይማኖት መሪዎች፥ ምሁራን፥ የሀገር ሽማግሌዎች፥ መንግሥትም አንድ ላይ ተሰብስበን ብሔራዊ ዕርቅ መደረግ አለበት። ቂም በቀል አያስፈልግም፥ ቂም ቂምን ይወልዳል እንጂ ትርፍ የለውም፥ ለልጆቻችን እና ለልጅ ልጆቻችን ኢትዮጵያ የምትባል ታላቅ ሀገርን እንጂ ቂም ልናወርሳችው አይገባም። የሀገራችን የነገ ዕጣ ፈንታዋ ምንድነው ማለት አለብን። ይህች ሀገር የመንግሥት ብቻ ስላልሆነች፥ ከመንግሥት ብቻ የሚመጣ መፍትሔ የለም። የሁላችንም ሀገር በመሆኗ ሁላችንም ተሰብስበን መፍትሔ ማምጣት ይኖርብናል። የምንናገረው እንደ ሃይማኖተኛ ነው፥ በሃይማኖት ችግሮች የሚፈቱት በይቅርታ ብቻ ነው። ጌታ ዓለምን ያሸነፈው በይቅርታ ነው፥ ይላል። ሉቃ፡፳፫፥ ፴፬። በመሆኑም ይቅርታ ሃይማኖታችንም ባህላችንም ነው፥ ከይቅርታ በላይ ምን አለ? ይቅርታ ለመንግሥትም ይጠቅመዋል፥ መሸነፍ አይደለም። ኔልሰን ማንዴላ ማሰርም መረሸንም ሲችል ይቅር በማለቱ ነው፥ ስሙ ከመቃብርም በላይ ሆኖ የደመቀው። መንግሥት እኮ አባት ነው፥ ሕዝብ ደግሞ የሥልጣን ባለቤት ነው፤በመሆኑም ለፈለገው ይሰጠዋል፥ ላልፈለገው ይነሳዋል፥ ድምፁን ይነፍገዋል። … ቅዱስ ሲኖዶስ የሚሰበሰበው በዓመት ሁለት ጊዜ ነው፥ ቢሆንም ዋናውን ሲኖዶስ ወክሎ የሚወስን ቋሚ ሲኖዶስ ስለአለ አሳሳቢነቱን ተመልክቶ የሕዝቡን ጥያቄ ለመንግሥት ማቅረብ አለበት። ያደርጉታልም ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ። የመንግሥት ባለሥልጣኖችም ቢሆኑ ልጆቻችን ናቸው፥ መመስገን በሚገባቸው ነገር እንደምናመሰግን ሁሉ መወቀስ በሚገባቸውም ነገር መውቀስ መንፈሳዊ ግዴታችን ነው። መከራ ሲመጣ ማንንም አይምርም፥ ሊቀ ካህናቱ ዔሊ ልጆቹን ባለመገሠጹ በእስራኤል ላይ መከራ መጥቶባቸዋል። ያ መከራ የዔሊንም የቤተ መቅደሱንም በር አንኳኵቷል። ሕዝቡ በጦርነቱ አልቋል፥ የዔሊ ሁለት ልጆች በጦርነቱ ላይ ሞተዋል፥ ታቦተ ጽዮንም ተማርካለች። ዔሊም ይህን ሁሉ መርዶ በአንድ ጊዜ በሰማበት ወቅት ከወንበሩ ወድቆ፥ አንገቱ ተቆልምሞ ሞቶአል። ፩ኛ፡ሳሙ፡፪፥ ፳፪-፴፮፤፬፥ ፩-፳፪። ስለዚህ ከርሱ ልንማር ይገባል፥ አለበለዚያ የመጣው ጎርፍ እኛንም ይዞ ይሄዳል። ይህ ሕዝብ ስለ ሁለት ነገር ወድዶ ፈቅዶ የሚሞት ሕዝብ ነው ወደ ኋላ የሚመልሰው ኃይል የለም። አንደኛ ስለ ሃይማኖቱ፥ ሁለተኛ ስለ ሀገሩ፤” ብለዋል።

ለብፁዕ አባታችን ረጅም የአገልግሎት ዘመን ከጤና ጋር ይስጥልን፥ በረከተቸው ይደርብን፥ አሜን።

የቃለ ምልሱን ሙሉ ውይይት ከዚህ ማግኘት ይቻላል፡- https://youtu.be/t-7T3wnda5k

Source:: http://www.adebabay.com/2017/12/blog-post.html

Categories

A sample text widget

Etiam pulvinar consectetur dolor sed malesuada. Ut convallis euismod dolor nec pretium. Nunc ut tristique massa.

Nam sodales mi vitae dolor ullamcorper et vulputate enim accumsan. Morbi orci magna, tincidunt vitae molestie nec, molestie at mi. Nulla nulla lorem, suscipit in posuere in, interdum non magna.